07/08/2026
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት 118.9 ቢሊየን ብር ገቢና 20.25 ቢሊየን ብር ትርፍ ማስመዝገቡን አስታወቀ
የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት በ2018 በጀት ዓመት (2025/26) 118.9 ቢሊየን ብር አጠቃላይ ገቢ በማስመዝገብ ከያዘው ዕቅድ 102.6 በመቶ ማሳካቱን አስታውቋል። ተቋሙ በዚሁ ዓመት 20.25 ቢሊየን ብር ትርፍ ማግኘቱም ተገልጿል።
የተቋሙ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ኢንጅነር ጌቱ ገረመው ዛሬ ነሐሴ 1 ቀን 2018 ዓ.ም. በሀያት ሪጀንሲ ሆቴል ለመገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ፣ ተቋሙ በበጀት ዓመቱ ከገቢ አሰባሰብ ጀምሮ እስከ ትርፍ ድረስ የሚታይ እመርታ ማሳየቱን ገልጸዋል።
በታክስ ክፍያም ተቋሙ ለመንግሥት 12.39 ቢሊየን ብር መክፈሉን የገለጹት ኢንጅነሩ፣ ይህ አፈጻጸም ከ2017 በጀት ዓመት ጋር ሲነጻጸር የ56 በመቶ ጭማሪ እንዳሳየ ጠቁመዋል።
በሌላ በኩል ተቋሙ በ2018 በጀት ዓመት 664 ሺህ 505 አዳዲስ የኤሌክትሪክ ደንበኞችን ማፍራቱን ገልጿል። በዚህም 205 የገጠር ከተሞች ለመጀመሪያ ጊዜ የኤሌክትሪክ አገልግሎት ተጠቃሚ ሆነዋል።
ኢንጅነር ጌቱ ገረመው እንዳሉት፣ በተለያዩ አካባቢዎች አልፎ አልፎ የሚያጋጥሙ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጦችን ለመቀነስ ሰፊ የኔትወርክ ማሻሻያና የመሠረተ ልማት ሥራዎች መከናወናቸውንም አስረድተዋል።