07/05/2026
Leadership dilemma
``````````````````````````````````
The best way to predict the future is to create it.
Abraham Lincoln
ሁልጊዜ መሪዎች በሁለት አስቸጋሪ ምርጫዎች መካከል ሚዛን ለመጠበቅ ይገደዳሉ። አንደኛ በሌላኛው የዓለም ጥግ የሚከናወኑ፣ ነገር ግን ውጤታቸው ዓለም ዐቀፋዊ አስከትሉት ያላቸዉ ጒዳዮች ሲሆኑ ሁለተኛው ወደ ፊት ሊከሰቱ ስለሚችሉ ጉዳዮች ወይም በአጭሩ የነገ ጒዳይ ነው። እጃችን ላይ በደርዜን የሚቈጠሩ አንገብጋቢ ችግሮች እያሉ የሩቁን ማሰብ ለምን አስፈለገ? የሚል ጥያቄ ነው። ወይም ዛሬ እጅግ አጣዳፊና ፋታ የሚነሡ ብዙ ችግሮች በዙሪያችን ሞልተው እያለ ስለማንኖርበት ነገ መጨነቊ የጤና ነው? ብሎ አንድ ሰው ሊጠይቅ ይችላል። እነዚህ ሁለት ጥያቄዎች የሚነሡት አንድም ዓለም ዐቀፋዊ ችግሮች ላይ ውይይት ሲደረግ አሊያም ወደ ፊት ሊከሰቱ ስለሚችሉ ችግሮች ላይ ትኲረት ሲደረግ ነው። ዓለም ዐቀፋዊም ሆነ የነገ ጒዳዮች ላይ እንደዚህ ዓይነት ጥያቄዎች መነሣታቸው ብዙ አይገርምም። ይኸ አስተሳሰብ አብዛኛው ሕዝብ የሚጋራው ነው። በርግጥም ለብዙ ዘመናት የነበሩ የሰው ልጆች ጥናት በአመዛኙ ትናንትናና ዛሬ ላይ ያተኮረ ነበር። የምናውቀው ስለ ወደፊት ወይም ነገ ብዙ ትኲረት ሲሰጥ አይስተዋልም።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ‘የነገ’ ጥናት ወይም “Future Study” (Futurology) በጣም ታዋቂ እየሆነ መቷል። ከዚህ በተጨማሪ ዓለም ሉላዊ ከመሆኗ የተነሣ ችግሮችን ለመፍታት በተናጥል የሚደረግ ሙከራ ቀርቶ በጋራ መወያየት ላይ ትኲረት ማድረግ የተሻለ አማራጭ እየሆነ ይገኛል። ከነዚህ ሙከራዎች መካከል አንዱ የሮም ክለብ (Club of Rome) የተሰኘ ቡድን በ1972 ዓ.ም ያሳተመው ሪፖርት ነው። በሪፖርቱ ላይ የሰው ልጆች ለሚኖሩበት ዓለም ያላቸው አስተሳሰብ ቀጥሎ ባለው ግራፍ አስቀምጠዋል።
(see the attached graph):-
ግራፉ በጊዜና (Time and Space) በቦታ የተዋቀረ ነው። ቊሙ መስመር (y co-ordinate) ቦታ (Space) የሚያመልክት ሲሆን አግዳሚው መስመር (x co-ordinate) ጊዜን (Time) ያመለክታል። ነጥብጣቦቹ ሰዎች ሲሆኑ በምን ጒዳዮች ላይ ትኲረት እንደሚያደርጒ ያሳያል። ብዙ ነጥብጣቦች ብዙ ሰው የሚያመለክቱ ሲሆን ዘርዘር ያሉ ነጥቦች ጥቂት ሰዎችን ያሳያሉ። ከግራፉ እንደምንረዳው አብዛኛው ሰው የቅርብ ጊዜ ችግሮችንና በአብዛኛው በራሱ ቤተሰብ ዙሪያ ብቻ የሚያውጠነጥን ነው። አብዛኛው ሰው ከጊዜ ዕለታዊ ችግሮች ላይ ብቻ ትኲረት የሚያደርግ ሲሆን ከቦታ አንጻር የራሱ ወይም የራሱ ቤተሰብ ጋር የተያያዙ ጒዳዮች ላይ ብቻ ትኲረት ያደርጋል። ጧት ከእንቅልፉ ተነሥቶ ወደ ዕለት ተግባሩ የሚሰማራው የዕለት ጒርሱን ለማሸንፍ ሊሆን ይችላል። በሌላ ጎን ደግሞ የሚሠራው የአጭር ጊዜ (ምናልባት የዛሬ ወይም የሳምንት) ጉርሻው እንዳይጎድልበት ሊሆን ይችላል። በጣም አሰበ ከተባለ የወሩ ወይም የዓመቱ የኑሮ ዋስትና ለማረጋገጥ ሊሆን ይችላል። ከራሱ ሕይወት አልፎ የሌሎችን ሰዎች ሕይወት በአዎንታዊ መልክ ለመለወጥ የሚያስብ ሰው በጣም ጥቂት ነው። እንዲሁም ከዛሬ አሻግሮ በመመልከት የትውልድ ጉዳይ የሚያሳስበው ሰው ብዙ አይደለም። በአጭር አገላለጽ ከራስና ከራስ ዘመድ አልፎ ለሌሎች የሰው ልጆች ማሰብ እንዲሁም ነገ የሚመጣውን ትውልድ እያሰበ የሚሠራ ሰው በጣም ጥቂት ነው።
እሩቅ የሚያስቡና የብዙ ሰዎች ሕይወት ለማሻሻል የሚጥሩ ሰዎች ቊጥራቸው እጅግ በጣም ጥቂት ነው። ከዛሬ ችግሮች በላይ አሻቅቦ ነገ ሊከሰት ስላለው ችግር ከወዲሁ ዝግጅት እንዲደረግ የሚያሳስብ ሰው ብዙ አይደለም። ከዚህ የተነሣ አንዳንድ ችግሮች በግልጽ ፈጥጠው እየታዩ እንኳን፣ አብዛኛው ሰው በቀጥታ እራሱን ወይም ቤተሰቡን የማይነካ ስለሚመስለው ግድ አይሰጠውም።
ብዙውን ጊዜ ወቅታዊ ችግሮች ላይ ብቻ አተኩሮ ነገ ሊከሰቱ የሚችሉ ችግሮችን ለመገመት አለመሞከር ችግሮቹ ድንገተኛ አደጋ ሆነው ከተፍ ብለው እንዲከሰቱ ምክንያት ይሆናል። ይኸ አካሄድ አጸፋዊ (Reactive) ምላሶችን ብቻ እንድንሰጥ ያስገድደናል። ችግሮች ይፈጠራሉ፣ ከዚያ በኋላ ለመፍትሔ እንሯሯጣለን። አንዳንድ ችግሮች ደግሞ ችግር ሆነው ሲታዩ ብዙ ብልሽት ካደረሱ በኋላ ስለሆነ መፍትሔያቸው ብዙ ዋጋ ያስከፍላል፣ መፍትሔው ተገኝቶ ከሆነ።
ተቋማትንም እንደ ሰዎች/ግለሰቦች መውሰድ እንችላለን። ሁልጊዜ በወቅታዊና ደራሽ ሥራዎች ላይ ብቻ ትኲረት የሚያደርግና ስልታዊ ዕቅዶች ላይ ትኲረት የማያደርግ ተቋም በዛሬው ዓለም በሕይወት መቀጠል አይችልም። በዚህ ዘመን ጠንካራና ዘመን ተሻጋሪ ተቋማትን ለመመሥረት ከሚያስፈልጒ ዋና ዋና ጉዳዮች መካከል ዓለም ዐቀፋዊ አውድን በተከተለ መልኲ እራሱን ሲያደራጅና ነገን በመገመት የተለያዩ የዕቅድ አማራጮችን ሲይዝ ነው። ይኸ አካሄደ ተለማጭነት (Adaptability) ይሰኛል። በ21ኛው ክፍለ ዘመን እጅግ አስፈላጊ ከሆኑ የመርነት ክህሎቶች መካከል አንዱ ነው። ዓለም ተለዋዋጭ በመሆኗ በአንድ ስልታዊ ዕቅድና እሳቤ ላይ ብቻ ተቸንክሮ መቆየት ዋጋ ያስከፍላል። ይልቊን ብዙ የይሆናል አማራጮችን ይዞ ሁሌ ለለውጥ መዘጋጀት የተሻለ አማራጭ ሆኖ ተገኝቷል። በአጋጣሚ የመጀመርያ አማራጭ ሳይሳካ ሲቀር ሁለተኛ አማራጭ ይወሰዳል። ይከሰታሉ ተብለው የሚገመቱ ችግሮች ቀድሞ (Scenario) ዝግጅት ስለሚደረግ አስከትሎቶቻቸው (impacts) ይቀንሳል።
ስለ ነገ ማሰብም ሆነ ዓለም ዐቀፋው አውድን ባማከለ መልኲ ችግሮችን መተንተን ማለት ወቅታዊ ችግሮችንና አካባቢያዊ ችግሮችን መዘንጋት ማለት አይደለም። ጊዜ የማይሰጡ አንገብጋቢ ችግሮችን እየፈቱ በዚያ ልክ ለችግሮቹ ዘላቂ መፍትሔ እያበጁ መሄድ የተሻለ አማራጭ ነው። አለበለዚያ በተመሳሳይ ችግሮች ላይ ዘመናትን የመፍጀት አዙሪት ውስጥ ይከታል። አንዳንድ ችግሮች በተፈጥሮአቸው ዓለም ዐቀፋዊ አውድን በመረዳት የሚፈቱ ናቸው።
ስለዚህ በዚህ ዘመን ያለ ማንኛውም ሰው፣ በተለይ በመርነት ደረጃ ያለ ሰው ዓለም ዐቀፋዊ አውድን የተገነዘበ፣ ዘላቂ መፍትሔ ማበጀት የሚችል ሰው መሆን ይኖርበታል። ጎበዝ የሆነ መር ከጠቅላላው ሕዝብ በተሻለ ሁኔታ ነገን አሻግሮ ማየት የሚችልና ከራሱ የግል ጥቅም አልፎ ለሰው ልጆች የጋራ ደህንነትና ሰላም መሥራት የሚችል ነው።