08/03/2026
ውድ የተዋህዶ ልጆች እንኳን ለዐብይ ጾም አራተኛ ሳምንት በሰላምና በጤና አደረሳችሁ
መፃጉዕ (የዐቢይ ጾም አራተኛ ሳምንት)
ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የማዳኑ ጉዳይ ጎልቶ ከሚነገርባቸው ጊዜያት አንዱ ይህ “መፃጉ’’ የተሰኘው ሳምንት ነው፡፡ “መፃጉ” ማለት በሽተኛ ማለት ነው፡፡ አምላካችን በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በዚህች ምድር ሲመላለስ ከደዌ ዳኛ ከአልጋ ቁራኛ የገላገላቸው መኾኑን የሚያሰረዱ የምስክርነት ቃሎች የሚሰሙበትን ጊዜ ቅዱስ ያሬድ “መፃጉ” በማለት ጠርቶታል፡፡
በመፃጉ ሳምንት የሚሰበከው ምስባክ፡- ‹‹እግዚአብሔር ይረድኦ ውስተ ዐራተ ሕማሙ፤ ወይመይጥ ሎቱ ኵሎ ምስካቤሁ እም ደዌሁ፤ አንሰእቤ እግዚኦ ተሣሃለኒ›› የሚለው ነው ፡፡ በመዝሙር 40 ላይ የሚገኘውን ይህንን ቃል ዲያቆኑ ከፍ ባለ ዜማ ከሰበከ በኋላ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 5 ላይ ያለው ይነበባል፤ ይተረጎማል ፡፡ በደዌ ሥጋም ኾነ በደዌ ነፍስ የተያዝን የሰው ልጆች የፈጣሪያችንን ምሕረትና ቸርነቱን እንደምናገኝ ተሰፋ የምናደርግባቸው ገቢረ ተአምራት ይሰማሉ፡፡
በአጠቃላይ እኛም ከዚህ ታሪክ ብዙ ነገሮችን እንማራለን፡፡ የመጀመርያው ሰውን መውደድን ማፍቀርን፣ ለሰው ድኅነት ብሎ ዝቅ ማለትን፣ ትሕትናን እንማራለን፡፡ የክርስትና ሕይወት የፍቅር፣ የሠላም፣ የአንድነት ሕይወት ነው፡፡ ለራስ ብቻ የሚኖሩት ሕይወት ሳይሆን ለሌሎችም መዳን ዝቅ ማለት ነውና እኛም ይህን በዓልን ስናከብር ጾሙንም ስንጾም ይህን ታሳቢ ማድረግ ይኖርብናል፡፡